Tuesday, February 4, 2014

የአማራውን ሕዝብ ክብር የደፈሩና ያዋረዱ አምባገነን ገዥዎች ለፍርድ ይቅረቡ!!!


thiopianReview
የአማራውን ሕዝብ ክብር የደፈሩና ያዋረዱ አምባገነን ገዥዎች ለፍርድ ይቅረቡ!!!
=================================
ከአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ(አንድነት) የተሰጠ መግለጫ
=================================
‹‹ጉድ ሳይሰማ…›› እንደሚባለው የኢትዮጵያ ሕዝብ በስርዓቱ እየተፈፀመበት ካለው ጭቆናና በደል፤ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብት ገፈፋ፤ አፈናና ስደት፤ ሙስናና የመልካም አስተዳደር እጦት በተጨማሪም በአምባገነን ገዥዎች እየተዋረደ፣ በአደባባይ እየተሰደበና ሰብዓዊ ክብሩ እየተጣሰ ይገኛል፡፡ እንዳለመታደል ሆኖም ሀገራችን ላይ ያለው ስርዓት ህዝቡን የሚያዋርድ፣ ከህዝብ ጥቅም ይልቅ ስልጣኑን የሚያስቀድም፣ ለህዝብ ጆሮ የሚሰጥ አስተዋይ መሪ የሌለው ነው፡፡ ለዘመናት ያልተፈቱ ችግሮችና በመሪዎቹ የሚፈጠሩ ችግሮች ትከሻውን ያጎበጡት የኢትዮጵያ ህዝብም ስርዓቱን ከነችግሩ መሸከሙ አልበቃ ብሎ መሪ ነን በሚሉት እየተበሻቀጠና ለውርደት እየተዳረገ ይገኛል፡፡

ፓርቲያችን በትኩረት እየተከታተለው ያለውና ሰሞኑን የተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያዎች ላይና በኢሳት ይፋ የተደረገው የአማራ ክልል ም/ ፕሬዘዳንትና የብአዴን ፅ/ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ አለምነው መኮንን የአማራውን ህዝብ በአደባባይ መሳደባቸውንና ማዋረዳቸውን የሚያሳዩ መረጃዎች መለቀቃቸውና የክልሉ መንግስት ለማስተባበል እንኳ ዝግጁ አለመሆኑ የሚያሳየው ንቀትንና ጥላቻን ብቻ ሳይሆን እንመራዋለን የሚሉት ህዝብ ትከሻ ላይ ተቀምጠው ፀረ ህዝብ አቋም እንደሚያራምዱ ነው፡፡ ፓርቲያችን የብአዴን/ኢህአዴግ ባለስልጣን በአማራ ህዝብ ላይ የፈፀሙትን ክብር የሚነካ አሳፋሪ ድርጊት በቸልታ ሊመለከተው እንደማይችል አስረግጦ ለመናገር ይወዳል፡፡ ፀረ ህዝብ አቋም የሚያራምዱ አምባገነኖችንም ከህዝብ ትክሻ ለማውረድ ትግሉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ያረጋግጣል፡፡ አንድነት በቅርቡ በጉራ ፈርዳና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ በዜጎች ላይ የተወሰደው የማፈናቀል ተግባር ስርዓቱና የስርዓቱ መሪዎች የፈጠሩት ችግር እንጅ የአካባቢው ሕዝብ የፈጠረው እንዳልሆነ ያምናል፡፡

አቶ አለምነው መኮንን የተባሉት ባለስልጣን የአለቆቻቸውን የዘወትር አባባል በማስረገጥ እመራዋለሁ የሚሉትን የአማራ ህዝብ ‹‹ሰንፋጭ የሆነ ትምክህተኝነት የተጠናወተው፣ ትምክህተኝነቱን ያልተወ፣ በባዶ እግሩ እየሄደ መርዝ ንግግር የሚናገር ወዘተ›› ካሉ በኋላ ‹‹የትምክህት ልጋጉን ማራገፍ አለበት›› በማለት እንደሌሎች ብሄረሰቦች ሁሉ ለዚች ሀገር ደከመኝ፣ ሰለቸኝ ሳይል ዋጋ የከፈለውን የአማራ ህዝብ ዋጋ በማሳጣትና የሌሎች ጠላት አድርጎ በማቅረብ የማጥላላት ዘመቻ ከፍተዋል፡፡
ፓርቲያችንም ይህንን አሳፋሪና የዜጎችን ክብር የደፈረ የባለስልጣኑ አባባል በቸልታ የሚታይ ሆኖ አላገኘውም፡፡
ስለዚህ፡-
1. ግለሰቡ በዚህ የተዛባ አመለካከቱ ለአማራ ህዝብ መሪ ሊሆን ስለማይችል በአስቸኳይ ከፓርቲና ከመንግስት ኃላፊነቱ እንዲነሳና ለህዝቡ ይፋ እንዲደረግ፤
2. ህዝቡን ያዋረደው ባለስልጣን ላይ ርምጃ የማይወሰድ ከሆነ ግን የግለሰቡ አመለካከት የብአዴንና የክልሉ መንግስት አቋም አድርገን የምንወስድ መሆኑ እንዲታወቅ፤
3. አንድነት ፓርቲ ፀረ-ህዝብ አቋም ያለው ግለሰብ ባደረገው የህዝብ ጥላቻ ንግግር (Hate speech) ተነስቶ ለሕግ የሚያቀርብ መሆኑ እንዲታወቅ፤
4. ፓርቲያችን ህዝቡን በማስተባበር በባህርዳር ከተማ ታላቅ የተቃውሞ ሰልፍ እንደሚጠራና ድርጊቱን የማውገዝና እንዲቆም የማድረግ ርምጃ የሚወስድ መሆኑን እንገልፃለን፡፡
ስለዚህ አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ የክልሉን ህዝብ እየመራው ያለው ብአዴን/ኢህአዴግ ለህዝብ ክብር የሌለው ድርጅት መሆኑን አውቆ ከፓቲያችን ጎን በመቆም እንዲታገለው ጥሪ እናቀርባለን፡፡
ዘላለማዊ ክብር ለኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን!!!
አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትሕ ፓርቲ (አንድነት)
ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, December 24, 2013

የአማራ ክልሉ “ዱላ ቅብብሎሽ” ግራ አጋባኝ እኮ!

“የመተካካት ሂደት የዱላ ቅብብሎሽ ነው”
አቶ አያሌው ጐበዜ “ዱላውን” ለማነው ያቀበሉት?

እናንተ … የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ነኝ የሚለው “CPJ” እና የሰብአዊ መብት ተከራካሪ ነኝ ባዩ “ሂዩማን ራይትስዎች” ከላያችን ላይ አንወርድም አሉን አይደል? (ከኢህአዴግና ከኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ማህበራት ላይ ማለቴ እኮ ነው!) እኔማ ባለፈው የአፍሪካ ሚዲያ ፎረም ሲካሄድ… ሦስቱ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ማህበራት፤ በጋራ የሰጡትን “ዱላቀረሽ” መግለጫ መስማታቸው ስለማይቀር አርፈው ይቀመጣሉ ብዬ ነበር፡፡ ችግሩ ግን “ጨው ለራስህ ስትል ጣፍጥ…” የሚለውን ተረት አያውቁትም!፡፡ አያችሁ … የመብት ተሟጋቾች እኮ ችኮ ናቸው፤ ነገር ከያዙ አይለቁም፡፡ መቼም መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ያደረጉት ሶስቱ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ማህበራት “የታሰረ አንድም ጋዜጠኛ የለም” ማለታቸውን የመብት ተሟጋቾቹ መስማታቸው አይቀርም፡፡ ግን ምን ያደርጋል? ሰሞኑን CPJ ባወጣው ሪፖርት፤ ጋዜጠኞችን በማሰር ኢትዮጵያን ከ10 የዓለም አገራት በሁለተኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧል (ገፅታ ለማበላሸት እኮ ነው!)
ድሮም ኒዮሊበራሊስቶች ለጦቢያ ተኝተው አያውቁም! እኔ ግን ሳስበው… እንዲህ ካሉት “ጃይንት” ዓለምአቀፍ ተቋማት ጋር ከመጋፈጥ ይልቅ “ፒስ” ማውረድ ነው ተመራጩ፡፡  (“አቅምን አውቆ መኖር ጥሩ ነው ታላቅ ችሎታ ነው” አለ መሐሙድ!)
ይኸውላችሁ…ኢህአዴግን ልማት ወጥሮ ይዞት ነው እንጂ CPJ ን ማሳመን አያቅተውም ነበር፡፡ ትዝ ይላችኋል …እነ IMF እና እና ዎርልድ ባንክ በባለሁለት ዲጂቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ከመንግስት ጋር ሲወዛገቡ! ኢህአዴግ ነፍሴ ምን አደረገ? 10 ዓመት ቢፈጅበትም አሳመናቸው! አሁን የኢህአዴግን ዕድገት እኮ  አምነዋል፡፡ ከጋዜጠኞች ተሟጋቾቹም ሆነ ከሰብዓዊ መብት ድርጅቱ ጋር ያለውንም ውዝግብ፤ ኢህአዴግ በውይይት ቢሞከረው ይሻላል ባይ ነኝ፡፡
እኔ የምለው…በመብራት፣ በውሃና በስልክ አገልግሎቶች አዲስ የተቆረቆርን አገር መሰልን አይደል? (ደቡብ ሱዳን እኮ ተሻለች!) ሰሞኑን በኢቴቪ የሰማሁት የውሃ ችግር ግን “የባሰ አለና አገርህን አትልቀቅ” የሚያሰኝ ነው፡፡ “ሰሜናዊቷ ኮከብ” እየተባለች በምትሞካሸው መቀሌ ከተማ 3 ወር ሙሉ ውሃ አልነበረም ተባለ፡፡ (አሁንስ የታለ?) የከተማዋ ነዋሪዎች ለኢቴቪ ቅሬታቸውን ሲናገሩ፤ በውሃ እጦት ክፉኛ መሰቃየታቸውን ገልፀዋል፡፡ (ግን እንደኛ ሳይማረሩ!) እኔማ… የመቀሌ ውሃና ፍሳሽ መ/ቤት፤ ተዘግቶ ነው ብዬ ተወራርጄ ነበር፡፡ አስበሉኝ!  ወዲያው የመ/ቤቱ ሃላፊ በኢቴቪ ከች አሉ (አለማፈራቸው!) እናም “የውሃ እጥረቱ የተከሰተው ከከተማዋ ዕድገት ጋር ተያይዞ ነው” ብለው በቀላሉ ተገላገሉት (ይሄማ የተበላ ዕቁብ ነው!)
“ስኳር ለምን ጠፋ?”
“ገበሬው ስኳር መጠቀም ስለጀመረ!”
“መብራት ለምን ይቆራረጣል?”
“የኢንዱስትሪ ዘርፉ ስላደገ!” እነዚህ ሁሉ ሰበቦች አሁን ፋሽናቸው አልፏል፡፡ (ሃላፊው አልሰሙማ!)
እንዴ… እነ መብራት ሃይልና የውሃና ፍሳሽ መ/ቤት ከተማውና ኢንዱስትሪው ሲያድግ የማንን ጐፈሬ እያበጠሩ ነበር? (አብረው አያድጉም እንዴ?) ወይስ የአገሪቱን ዕድገት እየተነበየ፣ ዕቅድ የሚያወጣ አዲስ መ/ቤት ማቋቋም ሊያስፈልግ ነው? (አሁንም እቅጯን ይናገሩ!)
እኔ ግን አንድ ሃሳብ አለኝ…ሦስቱ ትላልቅ የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት (ውሃና ፍሳሽ፣ መብራት ሃይል፣ ኢትዮ - ቴሌኮም) የኢኮኖሚ ዕድገቱና የከተሞች መስፋፋት ከአቅማቸው በላይ ስለሆነባቸው፣ ትንሽ የዕድገቱ ግስጋሴ በረድ…ቀዝቀዝ … ቢልላቸው ጥሩ ነው (ሌላው ለጥጦ ያቅዳል እነሱ …) ይሄ እንግዲህ በቀና ልቦና ሲተነተን ነው፡፡ ግን ደግሞ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዳሉት፤ የSabotage (አሻጥር) ነገር ሊኖርበትም ይችላል፡፡ ምናልባትም የኒዮሊበራሊዝም አቀንቃኞች ሰርገው ገብተው ይሆናል፡፡ (መረጃ ውድ በሆነበት አገር ሃሜትና ጥርጣሬ ቢነግስ አይገርምም!)
እኔ የምለው ግን…አፄ ምኒልክ ድንገት ቀና ብለው ይሄን ሁሉ “ምስቅልቅል” ቢመለከቱ “የት አገር ነው የነቃሁት” ብለው ግር የሚላቸው አይመስላችሁም? ከአንድ ክ/ዘመን በኋላ ጦቢያን እንደ አውሮፓ ሆና አገኛታለሁ ሲሉ፣ ከጥንቱም ብሳ ሦስት ወር ውሃ የሚጠፋባት አጃኢብ አገር ሆናላቸዋለች (እንዴት እንደሚያፍሩብን!)
በነገራችሁ ላይ…ካዛንቺስ አካባቢ ባለገመዱ ስልክና የኢንተርኔት አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ከተቋረጠ ድፍን ወር ሞላው፡፡ ምኒልክ ቢኖሩ … “ማርያምን አልምርህም!” ይሉን ነበር፡፡ እናላችሁ…ኢትዮ ቴሌኮም በተደጋጋሚ ደውለን (በሞባይላችን ማለቴ ነው!) ስንጠይቅ የተሰጠን ምላሽ ምን መሰላችሁ? “አገልግሎቱ የተቋረጠው ከመንገድ ሥራው ጋር በተያያዘ ስለሆነ ትንሽ ታገሱ” የሚል ነው (ኧረ ተመስገን ነው! መዘለፍም አለ እኮ!) እኔ የምለው ግን… “ትንሽ ታገሱ” ሲባል ምን ማለት ነው? 1 ወር? (ወርማ ሊያልፈን ነው!) 2 ወር? 1 ዓመት? 5 ዓመት? (አልነገሩንማ!) ለጊዜው ግን እኛም የመንገድ ሥራ ማለት “ልማት” እንደሆነ ስለምናውቅ፣ የመንግስት ልማት ከሚስተጓጐል የእኛ ልማት አፈር ድሜ ይብላ ብለን ልንታገስ ተስማማን (ምርጫ የለንማ!) ምን ትዝ አለኝ መሰላችሁ? የዛሬ ዓመት ገደማ የኢትዮ-ቴሌኮም ከፍተኛ ሃላፊ፤ ከኔትዎርክ ችግር ጋር ተያይዞ ለቀረበላቸው ጥያቄ፣ የመንገዱን መቆፋፈር እንደምክንያት ሊያቀርቡ አሰቡና፣ የፓርቲያቸውን ግምገማ ፈሩ መሰለኝ፣ እንዲህ በብልሃት ተናገሩ:- “ከተማዋ ምስቅልቅል ላይ ናት…ግን የዕድገት ምስቅልቅል ነው!” (ከማንኛውም ምስቅልቅል ያውጣን!)
እኔ የምለው ግን … ይሄ ለሁሉ ነገር እንደ ፍቱን መድሃኒት የሚታዘዘው የ1ለ5 አደረጃጀት (በቤት ስሙ “ጥርነፋ!”) በቴሌ፣ በውሃና ፍሳሽ፣ እንዲሁም በመብራት ሃይል አልተሞከረም እንዴ? (1ለ5 ያልገባበት የለም ብዬ እኮ ነው!) በቅርቡ እንደውም ይሄ አደረጃጀት ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መግባቱን የፖለቲካል ሳይንስ ምሁሩና የመድረክ ፓርቲ አመራር አባል የሆኑት ዶ/ር መረራ ጉዲና ተናግረዋል (የአካዳሚ ነፃነት ውሃ በላው እንዴ?) ግን እኮ እዚህ እንደውም ዘግይቷል፡፡ በየክልሉ ባሉ ዩኒቨርስቲዎች፣ የ1ለ5 አደረጃጀት ሥራ ላይ ተተግብሮ አመርቲ ውጤት እንዳመጣ፣ በኢቴቪ መስኮት ብቅ የሚሉ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች እየመሰከሩ ነው (ካድሬ ናቸው እንዳትሉኝ!) ዝም ብዬ ሳስበው (መረጃ የለማ!) 1ለ5 ለተማሪዎች እንኳን ሳይበጅ አይቀርም (ለፖለቲካ ቅስቀሳ ሳይሆን ለጥናት!) ችግር የሚመጣው አንድ ፕሮፌሰር ከአምስት ዶክተር ጋር ይጠርነፍ ሲባል ነው (እዚህ አገር ፍሬን የለማ!) እናም በዚያው ከቀጠለ… አንድ ከፍተኛ ባለሃብት ከአምስት መካከለኛ ባለሃብቶች ጋር ይጠርነፍ መባሉ አይቀርም (ቀይ መስመር ማለፍ ተለምዶ የለ!)
ይሄን ፖለቲካዊ ወግ እየከተብኩ ሳለ፤ “ኢቴቪ ወዳጄ” … አንድ ሰበር ዜና ሹክ አለኝ፡፡ ለስምንት ዓመት የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር በመሆን ያገለገሉት አቶ አያሌው ጐበዜ ባቀረቡት “የመተካካት ጥያቄ” መሰረት፣ አስቸኳይ ጉባኤ ተጠርቶ ሥልጣናቸውን ለምክትላቸው አስረከቡ አለኝ-ኢቴቪ! አይገርምም ፍጥነትና ቅልጥፍናቸው! የህዝብ አንገብጋቢ ጉዳዮችም አስቸኳይ ጉባኤ እየተጠራ እንዲህ አስቸኳይ እልባት ቢሰጣቸው አልኩ-በሃሳቤ፡፡ 24 ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ደግሞ ኢቴቪ ሌላ መረጃ አቀበለኝ፡፡ “የቀድሞው የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር የሙሉ አምባሳደርነት ሹመት ተሰጣቸው” የሚል፡፡ ሌላ ፍጥነት! ሌላ ቅልጥፍና! አትሉም (ከሮቦት ብቻ የሚጠበቅ!) “የመተካካት ሂደት የዱላ ቅብብሎሽ ነው” ያሉት አቶ አያሌው ጐበዜ፤ “ዱላውን ለሚቀጥሉት ወጣት አመራሮች አስረክቤአለሁ” ብለዋል፡፡
እኔን ያልገባኝ ምን መሰላችሁ? የዱላ ቅብብሉ ዓይነት! (ወደ ጐን  የዱላ ቅብብሎሽ አለ እንዴ?) ሌላም ያልገባኝ ነገር አለ፡፡ ወጣቱ ትውልድ ወይም New blood የሚባለው የትኛው ነው? አቶ አያሌው ጐበዜን የተኩት (የቀድሞው ምክትላቸውን ማለቴ ነው!) የአዲሱ ትውልድ አባል ናቸው እንዴ? (“ለሚቀጥሉት ወጣት አመራሮች አስረክቤአለሁ” ስለተባለ እኮ ነው!) በነገራችሁ ላይ ኢህአዴግ New blood የሚለው በስንት የእድሜ ክልል ውስጥ ያሉትን እንደሆነ ግልፅልፅ አድርጐ ቢነግረን ከ“ብዥታ” እንወጣለን፡፡ ወይም ደግሞ የዱላ ቅብብሎሽ ወደ ጐንም ይቻላል ብሎ እቅጩን ይንገረን፡፡ ያኔ አፋችንን ዘግተን እንቀመጣለን (እኔ New blood እንዳልሆንኩ ይታወቅልኝ!)
በመጨረሻ … አንድ ጥያቄ አለኝ፡ አቶ አያሌው ጐበዜ ስልጣናቸውን የለቀቁበትን ምክንያት በፌስ ቡክ ላይ ይፃፉልን!! (“ኢህአዴግ ፌስቡክ መጠቀም ያበረታታል” ሲባል ሰምቼ እኮ ነው!!)

 http://addisadmassnews.com

Tuesday, December 17, 2013

ጉቦ በመቀበል እስረኞችን የለቀቁ ታሰሩ!


ከ11 በላይ ታራሚዎችን በዚህ ሀሰተኛ ሰነድ ከእስር እንዲለቀቁ አድርገዋል
cuffs
ከ300 እስከ 500 ሺህ ብር እየተቀበሉ በሀሰተኛ ሰነድ ታራሚዎችን ከማረሚያ እንዲወጡ አስደርገዋል ተብለው የተጠረጠሩ ሶስት የአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት የስራ ሀላፊዎችና አምስት ተባባሪዎቻቸው በቁጥጥር ስር ውለው ፍርድ ቤት ቀረቡ።
ተጠርጣሪዎቹ ኦፊሰር ገብረመድህን አረጋ፣ ረዳት ኦፊሰር ኢሳያስ ከበደና ዋርደር ኢብራሂም መሀመድ ሲሆኑ፥ በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት የእስረኞች አስተዳደር የስራ ሃላፊዎችና ሰራተኞች ሆነው ሲሰሩ የነበሩ ናቸው።
ከእነዚህ የስራ ሃላፊዎች ጋር የጥቅም ትስስር በመፍጠር ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉት የተቀሩት ግለሰቦች ደግሞ ፥ በንግድ ስራ ይተዳደር የነበረው አቶ ሰለሞን ገለታ፣ አቶ ብሩክ ሀይሌ፣ ወይዘሪት ሳባ ገብረሚካኤል፣ አቶ ናታን ዘላለምና አቶ ቴዎድሮስ ግደይ ናቸው።
የፌደራሉ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን  መርማሪ ለፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ የወንጀል ችሎት ባቀረበው የጊዜ ቀጠሮ ማመልከቻ ላይ እንደተመለከተው፥ ከሳባ ገብረሚካኤል ውጪ እነዚህ በንግድ ስራ ይተዳደሩ የነበሩ ግለሰቦች ቀደም ሲል በተለያዩ ወንጀሎች ተፈርዶባቸውና በማረሚያ ቤት የእስራት ጊዜያቸውን ጨርሰው የወጡ ናቸው።
እንደ መርማሪው ማመልከቻ ሳባ ገብረሚካኤል በኮምፒውተር ፅሁፍ እያገዘቻቸው፥ በንግድ ስራ የሚተዳደሩት ግለሰቦችም ከፌደራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ታራሚዎች ከእስር የሚፈቱበትን ትዕዛዝ በሀሰተኛ መንገድ በማዘጋጀት እንዲሁም በሀሰተኛ ፊርማ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን ማህተም በማስመሰል አዘጋጅተዋል።
በማረሚያ ቤት የሚገኙና ቅጣታቸው ከአምስት ዓመት በታች ለሆነ 300 ሺህ ብር ከዚያ በላይ ከሆነ ደግሞ 500 ሺህ ብር እየተቀበሉ ፥ ከ11 በላይ ታራሚዎችን በዚህ ሀሰተኛ ሰነድ ከእስር እንዲለቀቁ አድርገዋል ይላል።
የሚያገኙትንም ገንዘብ ለኦፊሰር ገብረመድህን አረጋ፣ ረዳት ኦፊሰር ኢሳያስ ከበደና ዋርደር ኢብራሂም መሀመድ ለተባሉት የማረሚያ ቤቱ የስራ ሀላፊዎች በመስጠታቸው ነው በቁጥጥር ስር የዋሉት።
በመርማሪው ማመልከቻ መሰረት እነዚህ የስራ ሃላፊዎች የነበሩ ተጠርጣሪዎች የእስር መፍቻ ደብዳቤው በሀሰተኛ መንገድ የተዘጋጀ እንደሆነ እያወቁ ታራሚዎች እንዲፈቱ በማድረጋቸው ስልጣንን ያለአግባብ በመጠቀም የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ውለዋል።
ከሶስቱ የስራ ሀላፊዎች ውስጥ ኦፊሰር ገብረመድህን አረጋ ሀሰተኛ የእስር መፍቻ ካቀረበ አንድ ታራሚ 40 ሺህ ብር መቀበሉ ተመልክቷል።
የጊዜ ቀጠሮ ማመልከቻውን የተቀበለው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 2ኛ የወንጀል ችሎት ተጠርጣሪዎቹ ያቀረቡት የዋስትና መብት ጥያቄ ቢለቀቁ መረጃ ያጠፋሉ የሚለውን የመርማሪውን ተቃውሞ በመቀበል ፥ ጉዳያቸውን ማረሚያ ሆነው ይከታተሉ ብሏል። (ኤፍ.ቢ.ሲ)

የማንዴላ ሌላኛው ገፅታ!


በአይሁዶች ሚሽናህ ውስጥ “በእድሜ ዘመኑ የሰዎችን ልብ ደስ ለሚያሰኝ መልካም ስራ የተጋ፣ እነሆ የሌሎችን ቀንበር የተሸከመ፣ ከእርሱም ታላላቆችና ታናናሾች ለሆኑ ለወንዶችም ለሴቶችም ጠዋት በሆነ ጊዜ እንደሚገኝ ብርሃን የሆነ፣ እርሱ በሞቱም እንኳ ቢሆን በአምላክና በሰዎች ዘንድ እጅግ ይከብራል፣ ወደ ላይም ከፍ ከፍ ይላል፡፡” የሚል ቃል ሰፍሮ ይገኛል፡፡ ይህ ቅዱስ ቃል በኔልሰን ማንዴላ ተፈጽሞ እነሆ በዘመናችን ለማየት በቅተናል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ፣ መላ ደቡብ አፍሪካውያን ከፍ ባለ አክብሮትና ፍቅር “ማዲባ” እያሉ የሚጠሯቸው ኔልሰን ማንዴላ፤ በረጅሙ የትግል ህይወታቸው የፈፀሙት ስራ በመላእክት እንጂ በስጋ ለባሽ ሰው የሚፈፀም አይመስልም። የዘር መድልዎና የጭቆና አገዛዝ ቀንበር ተሸክመው፣ ወደር የሌለው ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉበት ያ ረጅሙና እጅግ አስቸጋሪው ጉዞአቸው ለዘመናት ሲገፋ ለኖረው ሰፊው ህዝባቸው፤ ከማለዳ ጀንበር በብዙ እጥፍ የደመቀ የነፃነትና የእኩልነት ብርሃን አብርቶላቸዋል፡፡
“የማይናወጥ ጽኑ እምነት ያለው ተራሮችን ማንቀሳቀስ ይችላል” ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተጠቀሰው፣ ለእኩልነትና ለአንድነት የነበራቸው መቼም የማይናወጥ ጽኑ እምነት፣ ቀናቶች ሁሉ እስኪያልቁ ድረስ ይገረሰስ የማይመስለው የአፓርታይድ የዘር መድልዎና የጭቆና አገዛዝ፣ እግራቸው ስር አይሆኑ ሆኖ እንዲፈረካከስ አድርጐታል፡፡
ከመላእክት እንጂ ከሰው ልጆች መቸም ቢሆን እንዲህ እንደዋዛ በማይገኘው እፁብ ድንቅ ርህራሄአቸውና ፍፁም ይቅር ባይነታቸው፣ ከዚህ በፊት የትም ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ፣ የህዝባቸውን የደቡብ አፍሪካውያንን ብቻ ሳይሆን ድፍን የአለማችንን ህዝብ ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ በከፍተኛ ፍቅርና አክብሮት መማረክ ችሏል፡፡ እነሆ በሞታቸውም ጊዜ ቢሆን በአምላካቸው ፊት በእጅጉ ተከብረው፣ በሰው ልጆች ዘንድም  አቻ በሌለው ከፍተኛ ፍቅርና ክብር እንደ ንስር ወደ ላይ፣ ወደ ሰማይ ከፍ፣ እጅግ ከፍ ብለዋል፡፡ ለዘጠና አምስት አመታት ያህል የዘለቀው የኔልሰን ማንዴላ ረጅም የትግል ህይወት፤ በችግርና በፈተና፣ በጽናትና በአይበገሬነት፣ በውድቀትና በድል ታሪኮች የተሞላ ነው ብሎ በቀላሉ መናገር ምናልባት የአንባቢን ንቃተ ህሊና አሳንሶ እንደመገመት ሊቆጠር ይችላል፡፡ ምክንያቱም የእሳቸው የህይወት ታሪክ እንደነዚህ ባሉ ታሪኮች የተሞላ መሆኑን ድፍን አለሙ በሚገባ ያውቀዋልና፡፡
ኔልሰን ማንዴላ፤ በአፓርታይድ አገዛዝ የእድሜ ልክ እስራት ተበይኖባቸው ሮቢን ደሴት በሚገኘው ጥብቅ ወህኒ ቤት ውስጥ ለሀያ ሰባት አመታት በእስር የማቀቁት የቀለም ትምህርት አሊያም የሙያ ክህሎት ስልጠና በመውሰድ ሳይሆን የኖራ ማዕድን በመቆፈር ነበር፡፡ ይህም ለተለያዩ የእፎይታና የመተንፈሻ አካላት በሽታ በከፍተኛ ሁኔታ አጋልጧቸዋል፡፡ ከሀያ ሰባት አመታት አስከፊ የእስር ቅጣት በሁዋላ ተፈተው፣ የሮቢን ደሴት ወህኒ ቤትን ለቀው ሲወጡ፣ ሳምባቸው በኖራ ብናኝ ክፉኛ ተጎድቶ በከፍተኛ የመተንፈስ ችግር እየተሰቃዩ ነበር፡፡ ይህም ብቻ አልነበረም፡፡ እስር ቤት ከገቡ ከአስራ አራተኛው አመት ጀምሮ ህይወታቸው እስካለፈበት ቀን ድረስ የእንባ አመንጪ እጢያቸው በኖራና በአስቤስቶስ ብናኝ ሙሉ በሙሉ በመጎዳቱ፣  ስሜታቸውን እንባ አውጥተው በማልቀስ መግለጽ አይችሉም ነበር፡፡
የቀድሞው የኬጂቢ ኮሎኔል፣ የዛሬው የራሺያ ቆፍጣና ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ ስለ ራግቢ ጨዋታ የፈለገውን ያህል ቢያወሯቸው ጨርሶ አይሞቃቸውም አይበርዳቸውም። የጂዶ ጨዋታን ነገር ካነሱላቸው ግን መላ ስሜታቸው የሚነቃውና ሰውነታቸውን የሚነዝራቸው ከመቅጽበት ነው።
የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜም የቅርጫት ኳስ ጨዋታ ነፍሳቸው ነው፡፡ አደባባይ ወጥተው ሲጫወቱ አይታዩ እንጂ የእረፍት ጊዜአቸውን በአብዛኛው የሚያሳልፉት ከመኖሪያ ቤታቸው ግቢ ውስጥ ከልጃቸው ጋር ነጭ ላብ እስኪያልባቸው  ድረስ የቅርጫት ኳስ በማልፋት ነው፡፡ እርግጥ ነው ማዲባ እንደ ቭላድሚር ፑቲን ጂዶ ሲታገሉ ወይንም እንደ ፖል ካጋሜ በመኖሪያ ቤታቸው ግቢ ውስጥ ከልጆቻቸውና ከልጅ ልጆቻቸው ጋር የቅርጫት ኳስ ሲጫወቱ ታይተው አያውቁም፡፡ ልጫወት ቢሉም የማያወላዳው ጤናቸው፣ ከተጫጫናቸው እርጅና ጋር ተዳምሮ ይህን መሰሉን እድል እንዳልሰጣቸው ይታወቃል። ይሁን እንጂ ሀገራቸው የአፍሪካና የአለም የእግር ኳስ ዋንጫ እንዲሁም የራግቢ የአለም ዋንጫ ውድድሮችን እንድታዘጋጅ ያደረጉት ጉልህ አስተዋጽኦ፣ አዘጋጅ ከሆነች በኋላም የሀገራቸውን ብሔራዊ የእግር ኳስና የራግቢ ቡድን ማሊያ ለብሰው ውድድሩ በሚካሄድበት ስታዲየም በመገኘት የሰጡት የሞቀ ድጋፍ፣ ብዙዎች ማንዴላ የእግር ኳስና የራግቢ ስፖርት ቅልጥ ያለ ደጋፊ ናቸው ብለው እንዲገምቷቸው አድርጓል፡፡
እውነቱ ግን ይህ አይደለም፡፡ ኔልሰን ማንዴላ የእግር ኳስም ሆነ የራግቢ ጨዋታ አድናቂ አልነበሩም፡፡ እርሳቸው የሚወዱትና የሚያደንቁት የስፖርት አይነት ቦክስና የረዥም ርቀት የሩጫ ውድድሮችን ብቻ ነበር፡፡ ሀያ ሠባት አመታትን ባሳለፉበት የሮቢን ደሴት ወህኒ ቤት ውስጥ ኖራና አስቤስቶስ ለመቆፈር ዶማና አካፋቸውን ይዘው ከመውጣታቸው በፊት ዘወትር ጧት ጧት የቦክስ ልምምድ ያደርጉ ነበር፡፡
“ረዥሙ የነፃነት ጉዞ” በሚል ርዕስ ባሳተሙትና የህይወት ታሪካቸውን በተረኩበት መጽሀፍ ውስጥ የቦክስ ስፖርትን ሲገልፁ “የቦክስ ስፖርት ሳይንሱ እንጂ ድብድቡ አዝናንቶኝ አያውቅም፡፡ አንዱ ራሱን ለመከላከል እንዴት ሰውነቱን እንደሚያንቀሳቅስ፣ ሌላው ደግሞ ለማጥቃትና ለመከላከል እንዴት ያለ ስትራተጂ እንደሚጠቀም፣ አንዱ ሌላኛውን እንዴት እንደሚቀድመው ሳይ ግን በጣም እገረም ነበር” በማለት ጽፈዋል፡፡
ለኔልሰን ማንዴላ የቦክስ ስፖርት ከዚህ ያለፈ ሌላ ትርጉምም ነበረው፡፡ ይህንንም በመጽሃፋቸው እንዲህ በማለት ገልፀውታል:- “የቦክስ ስፖርት ነፃና ዲሞክራሲያዊ ነው፡፡ በቦክስ ሪንግ ውስጥ ማዕረግ፣ እድሜ፣ ቀለምና ሀብት ምንም ቦታ የላቸውም፡፡ ፖለቲከኛ ከሆንኩ በኋላ የምሬን ተቧቅሼ አላውቅም፡፡ ዋናው ፍላጐቴ ልምምዱ ላይ ብቻ ነበር፡፡ አድካሚው ልምምድ ጭንቀትና ውጥረትን ማስተንፈሻ ድንቅ መሳሪያ ሆኖልኝ ነበር፡፡ ከባድ የቦክስ ልምምድ ካደረግሁ በኋላ አዕምሮዬንም ሆነ አካሌን ቅልል ይለው ነበር”
ኔልሰን ማንዴላ ለቦክስ ስፖርት የነበራቸውን ስሜት በመጽሀፋቸው ላይ በይፋ ከመግለፃቸው በፊት ዋልተር ሲሲሉስን ከመሳሰሉት የቅርብ የትግልና የእስር ቤት ጓዶቻቸው በቀር የሚያውቅ ሰው እምብዛም አልነበረም። የአለም የቦክስ ሻምፒዮን የነበረው አሜሪካዊው ሹገር ሬይ ሊዎናርድ፣ የአለም ሻምፒዮንነት ክብር የተቀዳጀበትን ቀበቶ በስጦታ ያበረከተላቸውም ይህንን ታሪካቸውን ጨርሶ ሳያውቅ ነው፡፡ ሹገር ሬይ ሊዎናርድ ያበረከተላቸው ይሄው የሻምፒዮንነት ቀበቶ፣ ሶዌቶ በሚገኘው የኔልሰን ማንዴላ ቤተሰብ ሙዚየም ውስጥ ተቀምጦ በጐብኝዎች እየታየ ይገኛል፡፡  ዛሬ ኔልሰን ማንዴላ የሚለው ስም በአለማችን አራቱም ማዕዘናት እንደ ጉድ የናኘና በቢሊዮን በሚቆጠሩ የአለማችን ህዝቦች ዘንድ በሚገባ የታወቀ መሆኑን አሌ ብሎ መከራከር ጨርሶ የሚያዋጣ አይደለም፡፡ ከ1926 ዓ.ም በፊት ግን የማንዴላ ወላጆች ሮሊህላህላ ማንዴላ እንጂ ኔልሰን ማንዴላ የሚል ስም ያወጡለት ወይም በዚህ ስም የተመዘገበ ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ለሁሉም ተማሪዎች የክርስቲያን ስም ማውጣት ይገባል በሚል ኔልሰን የሚለውን ስም ያወጣላቸው፣ የዘጠኝ አመት ብላቴናና የሜቶዲስት ቤተክርስቲያን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ሆነው ያስተምራቸው የነበረ መምህራቸው ነበር፡፡
ኔልሰን ማንዴላ ሲገረዙ የወጣላቸው ስም ዳሊ ቡንጋ የሚል ሲሆን ትርጉሙም የባህላዊው የቡንጋ አመራር አካል መስራች ማለት ነው፡፡ በአብዛኛው ደቡብ አፍሪካውያን ዘንድ በአክብሮት የሚጠሩበት “ማዲባ” ደግሞ የሚለው የጐሳ መጠሪያ ስማቸው ነው፡፡
ለኔልሰን ማንዴላ በተዘጋጀው የመታሰቢያ ስነ ስርአት ላይ ንግግር ካደረጉት መሪዎች አንዱ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ናቸው፡፡ እሳቸውም ኔልሰን ማንዴላ ለነፃነት ሲሉ የከፈሉትን መስዋዕትነት በማውሳት፣ አለም ከእሳቸው ህይወት ጠቃሚ ልምድ ሊቀስም ይገባል ብለዋል፡፡  እንደ እውነቱ ከሆነ እንደ ግለሰብ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ያደረጉት ንግግር እንከን የለሽ ነው፤ እንደ ሀገር ከታሰበ ግን በጣም ኮሚክ ነው። ለምን ቢባል የአፓይታይድን ስርአት ሲያራምድ ከነበረው የደቡብ አፍሪካ የነጮች መንግስት በበለጠ የኔልሰን ማንዴላን የነፃነት ትግል የተቃወመች፣ በመጨረሻም ኔልሰን ማንዴላ ኢትዮጵያ ውስጥ የተሰጣቸውን ወታደራዊ ስልጠና ጨርሰው ሀገራቸው እንደገቡ እግር በእግር ተከታትላ በቁጥጥር ስር እንዲውሉ፣ ከዚያም የእድሜ ልክ እስራት ተበይኖባቸው ለሀያ ሠባት አመታት በወህኒ ቤት እንዲማቅቁ ያስደረገችው አሜሪካ ስለነበረች ነው፡፡ ይህም አልበቃ ብሏት እስከ 2008 ዓ.ም ደረስ ኔልሰን ማንዴላንና ይመሩት የነበረውን የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ በአሸባሪና በአሸባሪ ድርጅትነት መዝግባ ይዛቸው ነበር፡፡
ኔልሰን ማንዴላ፤ ኮልፌ የፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም ውስጥ ለስድስት ወር የተሰጣቸውን ወታደራዊ ስልጠና አጠናቀው ሲመረቁ፣ ግርማዊ ቀዳማዊ ሀይለስላሴ ንጉሰ ነገስት ዘኢትዮጵያ ሽልማትም፣ ማስታወሻም የሚሆን አንድ ሽጉጥ ሰጥተዋቸው ነበር፡፡ ይህንን ሽጉጥ በቁጥጥር ስር ከመዋላቸው በፊት አንድ ሰዋራ ቦታ ላይ ቀብረውት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ኔልሰን ማንዴላ ከእስር ከተፈቱ በኋላ ከቀበሩበት ፈልገው ማግኘት አልቻሉም፡፡ ሽጉጡን ፈልጐ ማግኘት ከቻለ ሁለት ሚሊዮን ዶላር እሰጣለሁ ቢሉም ህይወታቸው እስካለፈበት ዕለት ድረስ አገኘሁ ያለ የለም፡፡ 

 http://addisadmassnews.com


እንደኔ እና እንደኔ ዘመን ልጆች…


- በኤሮግራም ደብዳቤ የተፃፃፋችሁ
- ራሺያ እጅ ስራ ተሰርቶ የመጣ ፎቶ ቤታችሁ የነበረ
- የካሴት ክር ለማጠንጠንና የምትፈልጉትን ዘፈን ለመስማት በእርሳስ ወይ በእስኪብርቶ ስታሽከረክሩ የዋላችሁ (ኤ እና ቢ የተምታታባችሁ፡ ወደፊት እና ወደ ኃላ የተደበላለቀባችሁ)
- የተቆለፈ ስልክ በሹካ፣ በፀጉር ማስያዣ ስትደውሉ እጅ ከፍንች የተያዛችሁ
- የማይክል ጃክሰንን "አይ አም ባድ" "አምቤ አምቤ" እያላችሁ ያቀነቀናችሁ፡ "ፋንኪ ታውን"ን "ኮቱም ጃኬቱም
ቆሽሿል "ብላች...ሁ ያስነካችሁ
- ፀጉራችሁን በእሳት በጋለ ሹካ የተተኮሳችሁ
- የሰኞ ጠዋት የግል ንፅህና ፍተሻ ያማረራችሁ
- ጠዋት ጠዋት ከኢትዮጵያ ሕዝብ መዝሙር ጋር "ኢንተርናሲዮናል"ን ልባችሁ እስኪፈርጥ ያቀነቀናችሁ፡
- "ጉልቴ ዘ ላንድ ሎርድ"፣ ሽልንጌን"፣ "የቡልቻ ልብ ነኝ"፣"አብዲሳ አጋ"፣ "ፋኖስና ኩራዝ "ከልባችሁ የቀረባችሁ
- "አፕሮች"፣ "ጋይድ "እና "ኮመን ሚስቴክ ኢን ኢንግሊሽ" የተባሉት መፅሃፍት መቼም የማይረሷችሁ
- ኮኮስ እየለቀለቃችሁ ያደጋችሁ
- የቢራ ጠርሙስ የሚመስለውን የፓራፊን ቅባት ክዳን በሚስማር የበሳችሁ
- እንሾሽላ ውስጥ እጅና እግራችሁ እስኪቃጠል የሞቃችሁ
- የአጥሚት ድስት ቂጥ እየተሻማችሁ የላሳችሁ
- ጆሯችሁን ተበስታችሁ ሰበዝ የሰካችሁ
- ቅልልቦሽ በየደረጃው ጣታችሁ እስኪፋፋቅ የተጫወታችሁ
- ቅጠል ቆርጣችሁ፣ በክር አስራችሁ፤ እግራችሁ እስኪጣመም ጢቢጢቢ የተጫወታችሁ
- ለኳስ መስሪያ የአባቶቻችሁን ካልሲ ከቁጥር ያጎደላችሁ
- ለሱዚ መጫወቻ የእናቶቻችሁን /የታላቅ እህታችሁን ስቶኪንግ አበላሽታችሁ የተገረፋችሁ
- በሾላ ላስቲክ ምን የመሰለ ኳስ የገነባችሁ
- ስልክ እንጨት ላይ ኳስ አስራችሁ ቴዘር የተጫወታችሁ
- ክረምትን በቆርኪ፣ በብይና በጠጠር ጨዋታ ያሳለፋችሁ
- በዱቤ ዱቄት ላስቲክ ደብተር የያዛችሁ
- በ" ሰይ ባንከረባብት"የብይ ሃብታችሁን ያደረጃችሁ
- አረንጓዴ- አረንጓዴ- ቢጫ- ቢጫ- ቀይ! አንዴም እየዘለላችሁ፣ አንዴም ቁጢጥ እያላችሁ፡ ከዚያም እንደስልክ እንጨት እየተገተራችሁ የፈነደቃችሁ
- አሌ ቡም የተጫወታችሁ
- የልጅነት ኩላሊታችሁ ከሹሌ እርግጫ የተረፈላችሁ
- በ”አኩኩሉ አልነጋም” ጨዋታ አልጋ ስር ተደብቃችሁ በዚያው እንቅልፍ ያሸለባችሁ
- "ፒቲ ጎል" ሰርታችሁ ኳስ የተራገጣችሁ
- የዛሬን አያድርገውና መጠጥ እንዲህ ሳይስፋፋ ሻሜታ በመጎንጨታችሁ የተገረፋችሁ
- ከባድ ጥፋት ፈፅማችሁ በሳማ የተለበለባችሁ፡ በርበሬ የታጠናችሁ
- እስኪብርቶና እርሳስ ጣቶቻችሁ መሃል ተደርጎ ክፉኛ የተቀጣችሁ፡ በባለእንጨቱ ማስመሪያ የተገረፋችሁ
- እጅ በጆሮ ይዛችሁ መቀመጫችሁ በቺንጋና በቁራጭ የውሃ ጎማ ያረረ

…እስቲ እንያችሁ!

ሕይወት እምሻው

Monday, December 16, 2013

”ፖለቲካ ሀጢአት ነው ወይ? ” የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሊቅ አጭር እና ግልፅ ምላሽ


በሳምንቱ መጨረሻ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ደብረዘይት ደብረ መድሃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስያን  ባዘጋጀው የመንፈሳዊ ጉዞ ላይ Gubaeበብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ምዕመናን ተሳትፈዋል።መርሃግብሩ ላይ ከምዕመናን እና በቀጥታ በማኅበራዊ ድህረገፆች ለአባቶች የጥያቄ እና መልስ መርሃግብር ተዘጋጅቶ ነበር። ለተነሱ ጥያቄዎች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ መስጠታቸው ከማኅበሩ የፌስ ቡክ ገፅ ላይ የተገኘው መረጃ ይገልፃል።ምእመናን ከእንደዚህ አይነት መርሃግብሮች እና ከሊቃውንቱ ቀጥተኛ እና  ትክክለኛ መረጃ ማግኘታቸው  ትልቅ ዋጋ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው።
ከገፁ ላይ የተገኘውን ከእዚህ በታች እንዲህ ይነበባል-
”ቀጥሎ የሚኖረን መርሐ ግብር የጥያቄና መልስ መርሐ ግብር ሲሆን ሊቃውንቱ መልአከ ታቦር ተሸመ ዘሪሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ አባል፤ መጋቤ ሐዲስ ደጉ ዓለም ካሣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ መጋቤ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉይና የሐዲስ ትርጓሜ መምህር፤ ሲሆኑ ከምዕመናን ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ደግሞ በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ አቅራቢነት ያስተናግዳሉ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ይመለስልን የምትሉት ጥያቄ ካላችሁ በውስጥ መስመራችንም ሆነ በ ኢ-ሜላችን ብትሉክልን እናስተናግደዋለን፡፡
……………………

ጥያቄ 2 . ቅዱስ ጳውሎስ ሀገራችን በሰማይ ነው ስላለ እኛ ክርስቲያኖች በምድራዊት ሀገራችን ላይ እንዴት እንስራ?

እግዚአብሔር ሰማይ ዙፋኔ ምድርም የእግሬ መረገ ናት እንዳለ አሁን ዛሬ ተቀምጠን የምንዘምርበት፣ የምንማርበት፣ የምናመሰግንበት፣ ይሄ ምድርም የእግዚአብሔር ፍጥረት ስለሆነ ሰው ለሀገሩም ሊሰራ ሊሞት ይገባዋል፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በአድዋ ድል የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንን ሱታፌ ማስታወስ በቂ ነው፡፡ መልአከ ታቦር ተሸመ ዘሪሁን የሊቃውንት ጉባኤ አባል ……………………..
ጥያቄ 4 ፡ ፖለቲካ ሀጢአት ነው ወይ?

ሰው በዚህ አለም ሲኖር ከሀጢአት በቀር በአለም ያለው ሁሉ ይመለከተዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እነ ዳዊት፣ እነሰሎሞን ፖለቲከኞች ነበሩ ስለዚህ ሀጢአት አይደለም ሀጢአት የሚሆነው አያያዙን ማወቅ ሲያቅት ነው፡፡ ወተት መጠጣት ሀጢአት አይደለም በረቡዕ ከተጠጣ ግን ሀጢአት ይሆናል፣ ቢላዎ ባለሞያ ሴት ካገኘችው ያገለግላል ባለጌ ካገኘው ሰው ይጎዳበታል ፖለቲካም አያያዙን ካወቅንበት ሀጢአት አይደለም፡፡ መጋቢ ሐዲስ እሸቱ ዓለምዓየሁ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉይና የሐዲስ ትርጓሜ መምህር።”
ምንጭ - https://www.facebook.com/mkidusan

የመዲናችን ገመናዎች በ‹‹ሮዛ›› መጽሐፍ ውስጥ ሲቃኙ



ባለፈው ሳምንት በዚሁ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ “በመዲናዋ ምስጢራዊ የወሲብ ገበያ ደርቷል” በሚል ርእስ በመታሰቢያ ካሳዬ የተጻፈውና በህብረተሰብ አምድ ላይ የተስተናገደው ጽሁፍ፣ ከሰሞኑ ከመጻሕፍት አዟሪዎች ደረት ላይ የማይጠፋውንና በማህበራዊ ድረ ገጾች ትኩስ መነጋገሪያ የሆነውን “ሮዛ” የተሰኘ መጽሀፍ አስታወሰኝ። ሁለቱም ጸሀፍት ለአብዛኞቻችን አዲስ አበቤዎች እንግዳ የሆኑና የማናውቃቸውን የመዲናችንን አስገራሚ ድብቅ እውነታዎች አስቃኝተውናል፡፡ የዛሬ ጽሁፌ አቢይ ትኩረት ግን “ሮዛ” በሚል ርእስ ለህትመት የበቃውን የሮዛ ይድነቃቸው የእለት ማስታወሻዎች ስብስብ መጽሀፍ ላይ ሂሳዊ ምልከታን ማቅረብ ነው፡፡
የእለት ማስታወሻዎች ተሰብስበው በመጽሀፍ መቅረባቸው በኢትዮጵያ ስነ-ጽሁፍ ውስጥ የተለመደ አይደለም፤ በቅርብ አመታት ውስጥ ለህትመት የበቁ የስመ-ጥር ኢትዮጵያውያን ግለ-ታሪክ መጻህፍት ከእለት ማስታወሻዎች ስለመጠናቀራቸው እስካሁን ያገኘሁት ተጨባጭ ፍንጭ የለም፡፡
ጎምቱው ደራሲ ተስፋዬ ገብረአብ ማንኛውንም የተለየ ቅጽበት ባስተዋለ ቁጥር ማስታወሻ ደብተሩን ከኪሱ አውጥቶ የመሰጠውን ቅጽበት፣ ሃሳብ ወይም ክስተት በዝርዝር የመጻፍ ቋሚ ልምድ እንደነበረው የቀድሞ የስራ ባልደረቦቹና ወዳጆቹ በአንድ አጋጣሚ አጫውተውኛል፡፡ ከነስህተትና ድብቅ አጀንዳቸውም ቢሆን ከነዚህ ማስታወሻዎች ተነስቶ “የጋዜጠኛው ማስታወሻ”፣”የደራሲው ማስታወሻ” እና “የስደተኛው ማስታወሻ” የተሰኙትን መጻህፍት ለህትመት እንዳበቃ ራሱ በስደተኛው ማስታወሻ ላይ ይገልጻል፡፡ ዛሬ ለዳሰሳ የመረጥኩት “ሮዛ” የሚል ስያሜ የተሰጠው መፅሐፍም ሮዛ በምትባል ኢትዮጵያዊት ኮማሪት የተጻፈ የግል ማስታወሻ ነው፡፡ ምንም እንኳ የግል ማስታወሻዎቿ አርታኢ እጅ ላይ ወድቀው መጠነኛ የይዘትና የቅርጽ ለውጦች ቢደረጉባቸውም የግል ማስታወሻዎችን ወደ መፅሐፍ ቀይሮ በማሳተም ረገድ ምናልባትም ቀዳሚ ስራ ነው ለማለት ያስደፍራል፡፡
ከዚህ የስነ ጽሁፍ ዘውግ ጋ ለመጀመሪያ ጊዜ በውል የተዋወቅነው አዶኒስ ከአመታት በፊት ወደ አማርኛ ተርጉሞ ባቀረበልን “The Diary of Ana Frank” (የአና ፍራንክ ማስታወሻ) በሚለው መጽሀፍ ይመስለኛል፡፡ አና እነዚህን በመላው አለም በበርካታ ቋንቋዎች ተተርጉመው በሚሊዮኖች ኮፒ የተሸጡላትን የእለት ማስታወሻዎች የከተበችው በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት በሆላንድ ርእሰ መዲና አምስተርዳም ከናዚዎች በተደበቀችባት ክፍል ውስጥ ነበር፡፡ በድርሰት ስራቸው የተደመምንባቸው በርካታ የአውሮፓ እና የአሜሪካ ደራሲያን ስራዎች ከደራሲያኑ የእለት ማስታወሻዎች የተወለዱ ነበሩ፡፡ ለአስረጅነት የቨርጂንያ ዉልፍን፣ አዳም ረታ በ”እቴ ሜቴ ሎሚ ሽታ” ድርሰቱ ውስጥ የሚያነሳትን ዝነኛዋ የኢሮቲክ ልቦለዶች ደራሲ የሆነችውን አናይስ ኒንን፣ ለየት ባሉት አጫጭር ልቦለዶቹ የሚታወቀውን ፍራንዝ ካፍካን፣ የዝነኞቹን አሜሪካዊያን የኢሮቲክና ሮማንቲክ ልቦለድ ደራሲዎቹን የኤሪካ ዮንግንና የሳንድራ ብራውንን ስራዎች ማንሳት እንችላለን፡፡
አናይስ ኒን “የኔም ሆነ የሌሎች እውነተኛ ማንነት በአንዳች አይነት የስሜት ጡዘት ወይም ቀውስ ውስጥ ስለሆነ እነዚህ ቅጽበቶች በምንም ሁኔታ እንዲያመልጡኝ አልፈቅድም፤ በፍጥነት አንዳች ሳላስቀር በእለት ማስታወሻዎቼ ላይ አሰፍራቸዋለሁ” ብላ ነበር፡፡ ፍራንዝ ካፍካ  “በህይወታችን የተለያዩ ምእራፎች ያሳለፍናቸውን የደስታና የሀዘን፣የጭንቀትና የፈንጠዝያ፣የድሎትና የውጣ-ውረድ ጊዜያት በእለት ማስታወሻዎቻችን በኩል መለስ ብለን ስንመለከታቸው በርግጥም መኖራችንን፣ ከመኖርም አልፈን የኖርነውን በጽሁፍ ለዘለቄታው ማስቀመጣችንን በውል እንገነዘባለን፤ ከእለት ማስታወሻችን በተሻለ የኖርነውን ህይወት፣ ቅጽበታዊ ስሜቶቻችንን ሳይቀር በግልጽነትና በታማኝነት የሚዘግብልን ድርሳን የለም” ይላል፡፡ ስመ - ጥሩ ደራሲ ዴቪድ ሴዳሪስ በበኩሉ “የእለት ማስታወሻዎቻችን ቢያንስ በሁለት  ምክንያቶች ይጠቅሙናል፤ ባለፈ ብስጭታችን፣ ስቃያችን፣ ስህተታችን፣ ድክመታችን፣ እንጭጭነታችንና ውጣ ውረዳችን ዘና እያልን እንዳንደግማቸው ትምህርት እንወስዳለን፤ ‘መጋቢት 3 ቀን 1998 ላይ እኮ እንዲህ ብለህ ነበር’ ብለን ክርክር በመጀመር ሙግት እንረታበታለን” ሲል ተናግሯል፡፡
ሮዛ ራሷም ለዳሰሳ በመረጥኩት ማስታወሻዋ ውስጥ እንደምትገልጸው ኮሌጅ የበጠሰች ሴተኛ አዳሪ ናት። ለሮዛ ዳዬሪዋ (የእለት ማስታወሻዋ) ብቸኛ የሚስጥር ጓደኛዋ የሆናት ይመስላል፤ ይህን የግል ማስታወሻዋን ነው እንግዲህ አደባባይ ያሰጣችው፡፡ በዚህች ምድር ላይ ገሚስ አድሜን ያሳለፈች የአገር ልጅ ለነገ ሳትል ጥብቅ ሚስጢሯን ሁሉ በመጸሐፍ መልክ ድንገት ስትዘከዝክ “ለምን?” ማለታችን አይቀርም፡፡ እኔም ለምን ብዬ ደጋግሜ ጠየቅኩ፡፡ መላምት እንጂ መልስ አላገኘሁም፡፡ ምናልባት ከብዙዎቹ ሴተኛ አዳሪዎች በተለየ ኮሌጅ መበጠሷ ህይወቷን ለሌሎች በማሳየት ማህበረሰባዊ ግዴታዋን ለመወጣት አስባ ይሆን?ምናልባት ሲሶ እድሜዋን የኖረችበትንና እሷ እምብዛም የማትቆጭበትን የቡና ቤት ህይወት በመተረክ ርካሽ ዝናን በአቋራጭ ለማግኘት አቅዳስ ይሆን? ነው ወይንስ ሙአመር ጋዳፊን ማግኘቷን እንደ ታላቅ ስኬት በመቁጠር እዩልኝ ስሙልኝ እያለችን ይሆን? እነዚህን ሁሉ መላምቶች ለመሰንዘር የተገደድኩት መጽሀፏ ውስጥ ምንም አይነት አስረጅ ባለማግኘቴ ነው፡፡ በመጸሐፉ የመጀመርያዎቹ ጥቂት ገጾች መረዳት የቻልኩት ሮዛ  ከያንዳንዱ የ ‹‹ሾርት›› እና የ‹‹አዳር›› ቢዝነስ በኃላ የዕለት ማስታወሻ የመያዝ ልምድ እንዳላት ብቻ ነው፡፡ ምናልባት መጸሐፉ የራሱ መግቢያ ተበጅቶለት ቢሆን ኖሮ እኛም ከመላምት በዳንንና ስለ ጸሐፊዋ ግብና ተልእኮ ብዙ መረዳት በቻልን ነበር እላለሁ፡፡ “ከሾፌር፣ ከሴተኛ አዳሪ፣ ከዘበኛና ከቤት ሰራተኛ የምታመልጥ አንዳችም የአለም ሚስጥር የለችም” በሚል መሪ ቃል ሽፋኑን ያደመቀው ይህ መጸሐፍ፤ ደራሲዋ የሙአመር ጋዳፊ ድንኳን ውስጥ የዘለቀች ‹‹ጀግና›› መሆኗን ገልጾ የልብ ምታችንን ያፈጥንብናል፡፡
በእርግጥ ይህ መጽሀፍ እስካሁን ካነበብኳቸውና ተመሳሳይ ይዘት ካላቸው መጻህፍት በብዙ መልኩ እንደተለየብኝ አልክድም፡፡ መጽሀፉ በርካታ አመታትን በዲፕሎማቶችና ከፍ ባለው ማህበረሰብ ዙርያ በሴተኛ አዳሪነት ህይወት ውስጥ ባሳለፈች፣ ከአንድም ሁለት ሶስት ዓለምአቀፍ ቋንቋ በምትናገር የተማረችና፣ ሯሷን በንባብ የገራች ኮማሪት መጻፉ ብቻ አይደለም ልዩ የሚያደርገው። አጻጻፏ በራሱ አንባቢ ላይ በግድ ቅጽበታዊ ስሜትን የማጋባት ባህሪ አለው፡፡ ስታዝን ይከፋናል፣ስትደሰት እንስቃለን፣ስትበግን እንንገበገባለን፣ ስትስቅ ፈገግ እንላለን…በማያገባን እያስገባችን ስሜታችንን ትሾፍረዋለች፡፡ እለታዊ ማስታወሻዋ የእንቶ ፈንቶ ጉዳይ ቢመስልም የዘመናችንን ማህበራዊ፣ፖለቲካዊ፣፣ባህላዊ፣ሃይማኖታዊና ስነልቦናዊ እውነታዎች በማስታወሻዎቿ በኩል በግርድፉ ታሳየናለች። ይህንን ደግሞ ከአንዲት ኮማሪት የምንጠብቀው ስላይደለ እንገረማለን፡፡ የቡና ቤት ሴት ሆናም የኛን የሞራልና መንፈሳዊ ዝቅጠታችንን ጥልቀት ስትነግረን እንድንሸማቀቅ አድርጋ ነው፡፡ በዕለት ማስታወሻዋ የመኝታ ገድሎቿን እየተረከችልን እሷን ሳይሆን እኛን እንድንታዘብ የሚያደርግ ስሜትን ትረጭብናለች፡፡ ይህንን ማድረግ የቻለችው ከልቧ በፍጹም የተቆርቋሪነት ስሜት ስለምትጽፍ ይሆናል፡፡ ከኪነ-ጥበብ ስራ በላይ ዘመንን ቅልብጭ አድርጎ የሚያሳይ ነገር ያለ አይመስለኝም ነበር፤ የፈጠራ ስራ ባልሆኑት የሮዛ የግል ማስታወሻዎች ውስጥ ይህንን ሁለንተናዊ የዘመን መንፈስ መመልከቴ ሳያስገርመኝ አልቀረም፡፡
“ሮዛ” እንደ “መሀልዬ መሀልይ ዘ ምናምን” እያሉ ከተድባበ ጥላሁን ቱባ ስራ በኋላ የልብ ካውያ እንደሆኑብን ገበያ ተኮር መጻህፍት የገድለ ወሲብ ጥርቅም አይደለም፤ ወይም ደግሞ ከጋዜጣ ወደ መጽሐፍ እንደተገለበጡት ስራዎች የቡና ቤት ሴቶችን ግልብ ቃለመጠይቅ ወደ ጽሁፍ ቀይሮ ለንባብ ያበቃም አይደለም፡፡ በእርግጥ እነዚህ መጻህፍትም ቢሆን ይብዛም ይነስ በተለያየ ዘመን እና ቦታ የተኖረን ህይወት ለዘለቄታው ለመጪዎቹ ትውልዶች የሚያስተላልፉ ቋሚ ሰነዶች እንደመሆናቸው ሚናቸውንና ጠቀሜታቸውን እያሳነስኩ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ። የስብሀት ገብረ እግዚአብሄር “ሌቱም አይነጋልኝ” መጽሀፍ ባይኖር በንጉሱ ዘመን በውቤ በረሀ የተኖረውን ህይወትና የዘመን መንፈስ እንዴት ማወቅ ይቻለን ነበር?የአለማየሁ ገላጋይ “አጥቢያ” ልቦለድ ባይኖር አሁን ሙሉ በሙሉ በፈረሰችው አራት ኪሎ ውስጥ የተኖረውን ህይወት፣የነበረውን ማህበራዊ መስተጋብር መጪዎቹ ትውልዶች እንዴት ሊያውቁ ይችላሉ? በማህበረሰብ ጥናት ዘርፍ የተሰማሩ ምሁራንስ ከተጻፉ መዛግብት በላይ ምን አይነት ተጨባጭ መነሻ ይኖራቸዋል?
ከላይ ከተጠቀሱት መጻህፍት በተለየ የሮዛ ህይወት በአንድ ሰፈር የተገደበ አይደለም፤የስራዋ ባህሪ ሆኖ መላው አዲስ አበባን ያካልላል፡፡ የሮዛ ህይወት ከድብቅ (ህቡእ)የመዲናችን የአስረሽ ምቺው ቪላዎች እስከ ሼራተን ቪላ እና የሊቢያው መሪ የጋዳፊ ድንኳን ድረስ ይዘልቃል፡፡ ጋዳፊ የአፍሪካ ህብረት አመታዊ ስብሰባን አስታከው የሀበሻ ቆነጃጅትን ለገዙት ‹‹ኤር አፍሪክ›› አየር መንገድ በሆስቴስነት ሲመለምሉ ሮዛ እንዳገኘቻቸው ትገልጻለች፡፡ ከሳቸው ጋርም ባረፉበት ሼራተን ቪላና በድንኳናቸው ውስጥአጭር ሆኖም አስገራሚ ቆይታ ማድረጓንም ትተርክልናለች፡፡ ሮዛ በመጸሕፏ እንደነገረችን ከሆነ ጋዳፊ በርግጥም ወፈፌ ነበሩ። ይህን ቆይታዋን “ከጋዳፊ ጋር ድንኳን መጋፈፍ” በሚለው የመጽሀፉ ሰፊ ምእራፍ ውስጥ በዝርዝር ገልጻዋለች፡፡ ከአመታት በፊት እዚሁ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ጋዳፊ በሼራተን ስላካሄዱት የሆስቴስ ምልመላ አጠቃላይ ሂደት በስፋት ማንበቤ ትዝ ይለኛል፡፡ምናልባት ሮዛ በዚሁ ምልመላ ወቅት አንዷ ታዳሚ መሆኗን መገመት ይቻላል፡፡
በ”ሮዛ”ውስጥ 29 በቀላሉ ከአእምሮ የማይጠፉ ታሪኮች አሉ፡፡ እንደገመትኩት አርታኢው በታሪኮቹ መረጣ ላይ ዋናውን ሚና ሳይወጣ አልቀረም፡፡ ምክንያቱም ለአመታት ከጻፈቻቸው በርካታ የእለት ማስታወሻዎች ውስጥ በሰው ዘንድ ልዩ ስሜት የሚፈጥሩትን ታሪኮች ለማወቅ ሙያዊ ትኩረትና ክህሎት ይፈልጋል፡፡
በ”ሮዛ” ውስጥ በመጀመሪያ ላይ የምናገኘው ታሪክ “ኮሌጅ በጠስን” የሚለውን ነው፡፡ ሮዛ በዚህ ታሪክ ውስጥ የትምህርት ፖሊሲያችን የደረሰበትን ዝቅጠት፣ የራሷንና የኮሌጅ ጓደኞቿን ህይወት በማውሳት ታሳያለች፤
…ኮሌጅ የበጠሱ የኔ “ባቾች” እንዳሁን ዘመን ተመራቂዎች ሁሉም ኮብልስቶን አንጣፊ አልሆኑም፡፡ በባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች ውስጥ አልጋ አንጣፊ የሆኑም አሉ፡፡ እንደኔ እና እንደወይንሸት የተማረ ሸሌ ሆነው የቀሩም አሉ፡፡ እንደ መዲና፣እንደ ራሄል፣እንደ ሂዊ፣እንደ ፎዚያ፣ እንደ ጠይባ አረብ አገር ለግርድና የሄዱም አሉ፡፡ እንደ አብዱልሰመድ(ወሎዬው) በአካውንቲንግ ተመርቀው የመን አገር ፍየል ለማገድ የተሰደዱም አሉ፡፡እንደ ምስኪኑ ሀብትሽ ሰፈር ውስጥ ጸጉር አስተካካይ የሆኑም አሉ፡፡ ሀብትሽ “ አታካብዱ ያው ነው፣ድሮም በጭንቅላቴ ነበር የምሸመድደው አሁንም ጭንቅላት ነው የምከረክመው፤አሁንም ድሮም ከአንገት በላይ ስፔሻሊስት ነኝ!” እያለ ራሱ ላይ ይቀልዳል፡፡ የክላስ ልጆችን ሳስብ እንደ ሀብትሽ አንጀቴን የሚበላኝ ሰው የለም፡፡ ሀብትሽ ለአራት አመት “ስፔስ” እየተመላለሰ፣አይኑ እየተጨናበሰ፣እንቅልፍ እንዳያሸንፈው እግሩን በሳፋ እየዘፈዘፈ፣ ሌት-ተቀን ትምህርቱን ሲሸመድድ ቢኖርም ያቺ ቆሽማዳ ህይወቱ ፈቀቅ አላለችም…(ገጽ-5)
በመጽሀፉ ውስጥ “ዋለልኝ” በሚለው ታሪክ ውስጥ አቸኖ የተባለውን የቺቺንያ ለማኝ እናገኛለን፤ዋለልኝ እንግሊዝ ለንደን ውስጥ በሚገኝ አንድ ግዙፍ ኩባንያ ውስጥ በስራ አስኪያጅነት የሚሰራና በርካታ ሺህ ፓውንድ ደሞዝ የሚከፈለው የቀድሞ የኢህአፓ አባል ነው፡፡ በኢህአፓ ትግል ወቅት በደረሰበት ስነ ልቦናዊ ችግር ምክንያት ወሲብ መፈጸም አይችልም፡፡ የሴት ገላ አቅፎ ለመተኛትም የቻለው በእንግሊዝ ቆይታው ረጅም ጊዜ በወሰደ የስነ ልቦና ህክምና ነው፡፡ በዚህ ቅንጭብ ታሪክ ውስጥ ሮዛ ተራ የህይወት ትዝብቷን እንዴት ከዘመናችን ማህበረ ፖለቲካ ጉዳዮች ጋር አቆራኝታ እንደምትመለከታቸው እንረዳለን፡፡ የሮዛ አንዳንድ ትዝብቶች አጥንታችን ድረስ ዘልቀው የሚሰሙን ናቸው፡፡ ለማሳያ ያህል የአቸኖን ቅንጭብ ታሪክ እንመልከት፡-
ሰኒና ወገቧን ያቀፋት ወጣት ኮንትራት ታክሲ ውስጥ ሊገቡ ሲሉ የእግር አልባው ለማኝ የአቸኖ ድምፅ ገታቸው። ከኋላቸው ስለነበርኩ ለማኙ ምን እንደሚላቸው እየተከታተልኩ ነበር፡፡ አቸኖ ሁሌም እንደሚያደርገው የሌሊቱን ብርድ ለመቋቋም በርካታ አረቄዎችን እንደተጋተ የድምጹ ቅላጼ ያሳብቃል፡፡
“አባቱ!እስቲ ብር ልቀቂብኝ!”
ወጣቱ ምንም ምጽዋት ሳይሰጠው ሰኒን እንዳቀፈ ወደ ታክሲው አመራ፡፡ አቸኖ ከመቅጽበት እሳት ለበሰ፤ሁልጊዜ ነው እንዲህ የሚሆነው፡፡ ሰው ሳይመጸውተው እንዳላየው ሆኖ ለማለፍ ሲሞክር ክፉ ይናገራል፤አቸኖ ሰኒን ያቀፈውን ወጣት ምን ሊለው እንደሚችል እየጠበቅኩ ነበር፡፡
“ትሰማኛለህ ወንድሜ!አንተ እንደዚህ በሰላም አየር የሴት ወገብ እንድታቅፍ እኮ ነው እኔ ባድመ ላይ በሻእቢያ ፈንጂ ሁለት እግሮቼን ያጣሁት! ተጸይፈኸኝ ነው ዞረህ እንኳን ልታየኝ ያልፈለግከው?”አለው፡፡
አቸኖ ምጽዋት ሲጠይቅ ለመላው ቺቺንያ በሚሰማ አስገምጋሚ ድምጽ እያንባረቀ ስለሆነ ያስፈራል…(ገጽ 111-112)
ሮዛ “የተከበሩ ማዳም ኤልዛቤጥ” በሚለው ታሪክ ውስጥ የማዳም ኤልዛቤጥ ግዙፍ የመስቀል ፍላወር ቪላ የሚሰጠውን ህቡእ የወሲብ አገልግሎትና በዚያም የሚደርሰውን አሰቃቂ አጋጣሚ በዕለት ማስታወሻዋ ታስቃኘናለች፡፡ ማዳም ኤልዛቤጥ የእድሜያቸውን ሲሶ በፈረንሳይ ያሳለፉ እመቤት ናቸው፡፡ ከዚህ ታሪክ በርግጥም በመዲናችን ውስጥ በርካታ የማናውቃቸው ገመናዎች መኖራቸውን እንረዳለን። ”ፍቅርተን ማን ገደላት?ባሏ” በሚለው አሳዛኝ ታሪክ ውስጥ ሮዛ የአፍ ወለምታ ህይወትን የሚያክል ውድ ነገር የሚያስቀስፍበትን ገጠመኝ ትነግረናለች፡፡
“ጥኡም ወዲ አስመራ” በሚለው ማስታወሻዋ ውስጥ አባትና ልጅ በአንድ ምሽት ሳያስቡት ከሷ ጋር ለመተኛት በሚያደርጉት ትግል ድንገት ግንባር ለግንባር መገጣጠማቸውን በመተረክ፣ የዘመናችንን እውነታ ፍንትው አድርጋ ታሳየናለች፡፡ ይህንን ታሪክ አንብቦ አለመደንገጥ ይከብዳል፡፡ “የቤዛ አልፋና ኦሜጋ” በሚለው ታሪክ ውስጥ ደግሞ ወንድም ከቡና ቤት ሴት ጋር እየቀበጠ ከበርካታ አመታት በፊት ከቤት ወጥታ የቀረች እህቱን፣ በዚያው ሆቴል ውስጥ በሴተኛ አዳሪነት ስትሰራ እንደሚያገኛት እንመለከታልን፡፡
የሮዛ የስራ ጸባይ በራሱ በየእለቱ ከተለያዩ የህይወት ጽንፍ የሚመጡ በርካታ ሰዎችን እንደሚያገናኛት ከመጽሀፉ እንረዳለን፡፡ በማስታወሻዎቿ ውስጥ ሮዛ ስለራሷ ገመና ብቻ አይደለም የምትተርክልን፡፡ ስለ ቡና ቤት ሴት ጓደኞቿ(የስራ ባልደረቦቿ)፣አብረዋት ስለተማሩ ወንዶችና ሴቶች፣ ስለፓይለትና ፕሮፌሰር ደምበኞቿ፣ በስካር ነብዘው በተንቋረረ ድምጻቸው “ከኛ በላይ ላሳር” ስለሚሉ ትምክህተኛ ምሁራን፣ስለአፍሪካ ዲፕሎማቶችና ሴሰኝነታቸው፣ራሳቸውን ከፓሪሱ “ኤፍል ታወር” በላይ ቆልለው ስለሚያዩ ዳያስፖራዎች…እያሳቀችን ትተርክልናለች። ደግሞ ማሳቅ ትችላለች፡፡ የስነ-ጽሁፍ አንዱ ግብ አንባቢን ማዝናናት መሆኑ ይታወቃል፡፡
”Usman The Pimp” በሚለው ታሪክ ውስጥ ብዙ አለም-አቀፍ ቋንቋዎችን አቀላጥፎ የሚናገረውን መልከ-መልካሙን አስጎበኚ ኡስማን እናገኛለን። ኡስማን በቅልጥፍናው በርካታ ሀበሻ ቆነጃጅትን ከአረቦች፣ከነጮች፣ከአፍሪካውያንና፣ከእስያውያን ቱሪስቶች ጋ ያገናኛል፤ሁሌም ባተሌና እረፍት አልባ ነው። የውጭ ዜጎቹን ከሀበሻ ቆነጃጅቱ ጋ የሚያገኛኝበት ህቡእ መረብ ስፋትና ጥልቀት በተለይ በአለም-አቀፍ ስብሰባዎች ወቅት አስገራሚ ነው፡፡ እኛ የዓለም ሶስተኛዋ የዲፕሎማሲ ዋና ከተማ እያልን የምናንቆለጳጵሳት መዲናችን፣ በእያንዳንዱ አለማቀፍ ስብሰባዎች ምሽት ታላቅ የወሲብ ንግድ እንደሚካሄድ የምንረዳው በዚሁ የኡስማን ዘ ፒምፕ ታሪክ ውስጥ ነው፡፡ የሴት ደላላ ሆኖ የተነገረን የኡስማን ታሪክ “ተወልጄ እድሜዬን ሁሉ በኖርኩባት አዲስ አበባ እንዴት ይሄ ሁሉ ጉድ መኖሩን እስካሁን አላወቅኩም?” ብዬ እንድጠይቅ አድርጎኛል፡፡ ሮዛ ከጋዳፊ የፕሮቶኮል ሀላፊ እና ከራሳቸው ከሊቢያው መሪ ጋር እንድትገናኝ አስፈላጊውን ሁኔታ ያመቻቸውም ይኸው ሴት አቅራቢ ኡስማን ዘ ፒምፕ ነው፡፡ ሮዛ ኢትዮጵያዊያን ሴት እህቶቻችን አረብ አገር ብቻ ሳይሆን እዚሁ በአገራችን ለወሲብ ገበያ በስፋት እንደሚቀርቡ ትነግረናለች፡፡ ሴቶቻችንን ለአረቦች በረብጣ ሪያል በመሸጥ ሀብት ንብረት ያፈሩ ሰዎችን ለማሳየትም ይህንኑ ዝናው በከተማዋ ቆነጃጅት ዘንድ የናኘውን ኡስማን ዘ ፒምፕን ታሪክ ታቀርብልናለች፡፡
“ራቁት ጭፈራ ቤቱ ተዘጋ” በሚለው ታሪክ ውስጥ ሮዛ ደምበል ህንጻ ስር ስለነበረው ’ኢን ኤንድ አውት’ ስለተባለውና ከበርካታ ዓመታት በፊት በፖሊስ አሰሳ ስለተዘጋው ራቁት ቤት ቆይታዋ ታወጋናለች፡፡ ይህ የራቁት ቤት በአሰሳ መልክ ሲዘጋ ኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ጨምሮ በበርካታ የአገራችን ሚዲያዎች በስፋት መዘገቡ ይታወሳል፡፡ በወቅቱ ጥቂት ስመጥር ምሁራንና አርቲስቶች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው እንደነበር ይታወሳል። ሮዛ የቤቱ ታዳሚዎች እነማን እንደነበሩ ብቻ ሳይሆን በዚሁ ህንጻ ውስጥ በሚገኝ ሊፍት ውስጥ ብዙ የወሲብ ገድሎች ይፈጸሙ እንደነበረ በምልሰት ትተርካለች፡፡ እንደምሳሌም ‹‹የሊፍት ቴክኒሻኑ ፈሌ›› በሚለው ንዑስ ርዕስ ስር ይሆናል ብለን የማናስበውን ድብቅ የሊፍት ውስጥ የቤርጎ አገልግሎት እናገኛለን፡፡
ከታሪክ ታሪክ የሮዛን ስሜት እየተጋራሁ ነው መጽሀፉን የጨረስኩት፡፡ ማስታወሻዎቹ በቀልድና በጨዋታ የተዋዙ ስለሆኑ አዝናንተውኛል፡፡ በየታሪኮቹ ጣልቃ በማህበረሰባችን ሁኔታ ያዘንኩባቸውና የደነገጥኩባቸው ቅጽበቶችም ነበሩ፡፡ 29ኙም ታሪኮች ስሜት ይነካሉ ማለት ይቻላል፡፡ የማስታወሻዎቹ ስነ-ጽሁፋዊ ውበትም ማለፊያ ነው፡፡የሮዛ ለየት ያሉ የህይወት ትዝብቶች፣ ምልከታዎችና ለማንኛውም ነገር ያላት በሳል አስተሳሰብ ይማርካል። አንዳንዶቹ ማስታወሻዎች የተጻፉበት ቀን ተገልጿል፤ በርካቶቹ መቼ እንደተጻፉ ግን አልተገለጸም፡፡ቀኑ ቢገለጽ በጊዜው ስለነበረው አጠቃላይ ሁኔታ እንድናውቅና ሌሎች ተዛማች ክስተቶችን እንድናሰላስል ይጋብዘን ነበር፡፡
ሮዛ ታሪኩን በስራ ቦታዋና በስራ ባልደረቦችዋ ቋንቋ በማቅረብዋ አልወቅሳትም፡፡ ግልጽነቷንና ታማኝነቷን አበረታታለሁ፡፡ መሸፋፈኑና መደባበቁ ነው ክፉኛ የጎዳን፡፡ ቃላት የሚጠበቅባቸውን ነገሮችን የመግለጽ ሚና በአግባቡ እስከተወጡ ድረስ ነውር አይሆኑም ብዬ አምናለሁ። ሮዛ “ሩካቤ ስጋ”፣”ግብረ ስጋ”፣”ተራክቦ ስጋ”፣”የጭን ገረድ”፣”የከንፈር ወዳጅ”፣”እቁባት” ወዘተ የሚሉ በስራ ገበታዋ ላይ ፍጹም የማትጠቀማቸውን ማለዘቢያና ማሽሞንሞኛ ቃላትን በማስታሻዎቿ ውስጥ ብትጠቀም ኖሮ አስመሳይ ትሆንብኝ ነበር። አርታኢዋም ይህን ነጻነቷን ስላልነፈጋት ምስጋናዬ ይድረሰው፡፡ ስለቡና ቤት ህይወት እየተወራ ቃላትን ማሽሞንሞን የመጽሀፉን ጠቅላላ መንፈስ የሚያውከው ይመስለኛል፡፡
ሮዛ የአዋቂ መጽሀፍ ነው፤እድሜያቸው ከ18 አመት በታች የሆኑ ታዳጊዎች እንዳያነቡት በሽፋኑ ላይ ተገልጿል። እንደ አደገኛ መድሀኒት ህጻናትና ታዳጊ ወጣቶች ከማይደርሱበት ቦታ መቀመጥ ይኖርበታል፡፡ ሆኖም ግን ይህ በሽፋኑ ላይ መገለጡ አደጋውን ሙሉ በሙሉ ያስወግዳል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ሁላችንም እንደምንረዳው፣ የእለት ማስታወሻዎች በባህሪያቸው ቅጽበታዊ ስሜቶች በትኩስ ስሜት፣ በማያመዛዝን ህሊና እና በጥድፊያ ወደ ጽሁፍነት የሚቀየሩ ሰዋዊ ትዝብቶች እንደመሆናቸው፣ ‹‹ሮዛ›› በዚህ ስሜት ውስጥ ሆና የከተበቻቸው ማስታወሻዎች በአፍላ እድሜ ላሉ ወጣቶች የሚያስተላልፉት መልዕክት አደጋው የትየሌሌ የሚሆንበት አጋጣሚ የሰፋ ነው። በመሆኑም በኔ ግምት የአርታኢው ሚና መሆን የነበረበት እነዚህን ስሜት ያናወጣቸው የግል ማስታወሻዎችን ማለዘብና ማስከን ብሎም ለአንባቢ የማይጎረብጡ፣ በማንኛውም ጊዜና ሁኔታ መነበብ የሚችሉ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ይህንን አርታኢው አሳክቶታል ብዬ አላምንም፡፡
ምክንያቱም የመፅሐፉ ስሜት አንባቢ ዘንድ ሲደርስም ቢሆን የልብ ምትን የሚያፈጥን፣ የቡና ቤት ሁካታው የሚሰማ፣ ፈንጠዚያው ያልበረደለት ሆኖ ነው፡፡  መጽሀፉ ውስጥ በርካታ የፊደል፣የቃላትና የሀሳብ አለመጣጣም ስህተቶች አሉ፡፡አርታኢው “ሮዛ በተለያየ አይነት ስሜት ውስጥ ሆና በተለያየ ቅጽበትና ጊዜ የጻፈቻቸው ማስታወሻዎች ስለሆኑ እንደፈለገች በመዘባረቅ መጻፏንና ያም ከነስህተቱ ማለፉን አንባቢዎች ይወዱታል፤ይረዱታል” የሚል አቋም ቢይዝ እንኳን መሰረታዊዎቹን ስህተቶች ማረም ነበረበት፡፡ ለምሳሌ “ሊሊ ቂጦ” በሚለው ታሪክ ውስጥ ሊሊን አንዳንድ ቦታ ላይ ሚሚ ሆና እናገኛታለን፡፡”የቤዛ አልፋና ኦሜጋ” በሚለው ታሪክ ውስጥ ታሪኩ የሚከወንበት  ኦሜጋ ሆቴል አንድ ቦታ ላይ ኦሜድላ ሆቴል ተብሎ እናገኘዋለን፡፡” የሚልኪና የሹገር ማሚዎቹ አጭር የህይወት ታሪክ” በሚለው ታሪክ ውስጥ ወይዘሮ ሳሮን በምን አስማት ቲና እንደምትሆን ግልጽ አይደለም፡፡ ምናልባት እነዚህ ስህተቶች አርታኢውን ሰነፍ ያስብሉት ይሆን እንጂ ጸሐፊዋን ክፉኛ የሚያስተቹ ናቸው ለማለት አልደፍርም፡፡
 በተለያየ ውጥንቅጥ ስሜት ውስጥ ሆነን ክስተቱን ለማስቀረት ብቻ እንዳሻን ስለምንጽፍ (ዲያሪ የመጻፍ ልምድ ካለን)በሌላ ጊዜ በተረጋጋ ስሜት ውስጥ ሆነን ስንመለከታቸው እንዲህ አይነት ተራ፣አስቂኝና አዝናኝ ስህተቶችን እንደምንፈጽም ባልዘነጋውም አርታኢው የሮዛን ስህተቶች ማለፍ አልነበረበትም ባይ ነኝ፡፡ አርታኢው “የእለት ማስታወሻ ከነስህተቱ ነው የሚያምረው፤አለበለዚያ ለዛውንና ወጥነቱን ያጣል” የሚል አቋም ያለው አይመስለኝም፡፡ መጽሀፍ ላይ ሁሉም አይነት ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል፡፡በቀጣይ እትሞች ላይ እነዚህ ስህተቶች እንደሚታረሙ እምነቴ የፀና ነው፡፡

addisadmas